የምክርቤቱ ጸሀፊና የአፈጉባኤ ጽ/ቤት ሀላፊ
የድሬደዋ አስተዳደር ምክር ቤት ጸሀፊ ስልጣንና ተግባር፡-
በቻርተሩ አንቀጽ ፲፰ የተደነገገው እንደተጠበቀ ሆኖ የምክር ቤት ፀሐፊ ለአፈ-ጉባኤው ተጠሪ ሆኖ የሚከተሉት ስልጣን እና ተግባራት ይኖሩታል፡-
፩) የምክር ቤቱን ስብሰባዎች ቃለ-ጉባኤዎች ይይዛል፣ ተከታታይ ቁጥር እየሰጠ ያደራጃል፣
፪) የምክር ቤቱን ኮሚቴዎች ቃለ-ጉባኤዎች እና ሰነዶች እንዲጠበቁ ያደርጋል፣ ለአባላት ቃለ-ጉባኤ ያሰራጫል፣
፫) የምክር ቤቱ አስተባባሪ ኮሚቴ ፀሐፊ በመሆን ያገለግላል፣
፬) በአፈ-ጉባኤው የሚሰጡትን ሌሎች ተግባሮች ያከናውናል፡፡
የምክር ቤት ጽ/ቤት ሀላፊ
የጽህፈት ቤቱ ስልጣንና ተግባር
ጽህፈት ቤቱ የሚከተሉት ስልጣንና ተግባራት ይኖሩታል፡-
፩. ለምክር ቤቱና ምክር ቤቱ ለሚያቋቁማቸው ኮሚቴዎችና አደረጃጀቶች አጠቃላይ ሙያዊ ድጋፍና አስተዳደራዊ አገልግሎት ይሰጣል፤
፪. በምክር ቤቱ አባላት እና አካላት ለሚከናወኑ የህግ ማውጣት፣ የክትትልና ቁጥጥር እና የህዝብ ውክልና ስራዎች ሙያዊ ድጋፍ ይሰጣል፤
፫. በአስተዳደሩ በየደረጃው የሚገኙ የህዝብ ምክር ቤቶች የማስፈጸም አቅም የሚጠናከርበትን ስልት በማውጣት ስራ ላይ ያውላል፤
፬. ለምክር ቤቱ ጠቅላላጉባኤና ልዩ ልዩ ኮሚቴዎች የሚያስፈልጉትን የመሰብሰቢያ አዳራሾች ያደራጃል፤
፭. የምክር ቤቱን ቃለ-ጉባኤዎች፣ ውሳኔዎችና ሰነዶች በሚገባ ተመዝግበው እንዲጠበቁ ያደርጋል፡፡
፮.ለምክር ቤቱ አባላትና አካላት የቤተ-መጻሀፍት፣ የምርምርና የመረጃ አገልግሎት ይሰጣል፤
፯. ምክር ቤቱ ያጸደቃቸውን ህጎች በድሬ ነጋሪት ጋዜጣ እንዲታተሙ ያደርጋል፤ የምክር ቤቱን መጽሔቶችና ጋዜጦች ህትመትና ስርጭት ይከታተላል፤
፰. አፈ-ጉባዔው በሚሰጠው አመራር መሰረት ለምክር ቤቱ እንግዶች አስፈላጊውን የመስተንግዶ አገልግሎት እንዲያገኙ ያደርጋል፤
፱. ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በመመካከር ፀጥታና ደህንነት መከበሩን ይከታተላል፣ በማንኛውም የምክር ቤቱ ቅጥር ግቢ ፀጥታና ሥነ-ሥርዓት መከበሩን ያረጋግጣል፤
፲. ለምክር ቤቱ አባላት እና አካላት በህግ የተወሰኑ ጥቅማ ጥቅሞችን እና ልዩ መብቶችን ያስፈጽማል፡፡
፲፩. በተለያዩ የሙያ ዘርፎችና ጉዳዮች ላይ ለምክር ቤቱ እና ለአካላቱ የማማከር አገልግሎት ይሰጣል፣ የጥናትና ምርምር ስራዎችን ይሰራል፤
፲፪. የምክር ቤቱን ስራዎችና የምክር ቤቱን ስልጣን እና ተግባር የሚመለከቱ ጉዳዮችን በተመለከተ ዜናዎችንና መዋእለ ዜናዎችን ያሰባስባል፤ ያዘጋጃል፤ የተለያዩ ፕሮግራሞችን በማዘጋጀት በሬዲዮ፣ በቴሌቪዥን በድረ-ገጽና በልዩ ልዩ ዘዴዎች ያሰራጫል፤
፲፫. የአቅም ግንባታ ስራዎችን ይሰራል፤
፲፬. የንብረት ባለቤት ይሆናል፤ ውል ይዋዋላል በስሙ ይከሳል ይከሰሳል፤
፲፭ የምክር ቤቱን አካላትና አባላት ሥራ ለማሳካት የሚረዱ እና በአፈ-ጉባኤው የሚሰጡ ሌሎች ተግባራትን ያከናውናል፡፡